ሄዝቦላህ የተኩስ አቁሙ “በመጣሱ” በእስራኤል ላይ ጥቃት መፈጸሙን ገለጸ
በሊባኖስ የሚገኘው የሺዓ እስልምና ፖለቲካዊ እና ወታደራዊ ቡድን ሄዝቦላህ፤ እስራኤል በአሜሪካ እና በኢራን ተደረሰውን የተኩስ አቁም ስምምነት “በመጣሷ” በአገሪቱ ሰሜናዊ ክፍል የሚገኝ ከተማ ላይ ጥቃት መፈጸሙን አስታወቀ።
ሄዝቦላህ እንደገለጸው ሮኬቶችን የተኮሰው በእስራኤል እና በሊባኖስ ድንበር አቅራቢያ ወደሚገኘው ኪርያት ሽሞና እንዲሁም በሰሜናዊ እስራኤል ሚስጋቭ አም አካባቢ ነው።
“እስራኤል እና አሜሪካ በአገራችን እና በሕዝባችን ላይ የሚፈጽሙት ጥቃት እስከሚቆም ድረስ ይሄ ምላሽ ይቀጥላል” ብሏል።
አሜሪካ እና ኢራን የመካከለኛው ምሥራቅ ጦርነትን ለማስቆም የሁለት ሳምንት ተኩስ አቁም ላይ ቢደርሱም እስራኤል በሊባኖስ ውስጥ የምታካሂደው ጥቃት ቀጥሏል። ኢራን እና አሸማጋይዋ ፓኪስታን የተኩስ አቁሙ ሊባኖስንም እንደሚያካትት ገልጸዋል። አሜሪካ እና እስራኤል በበኩላቸው ሊባኖስ የስምምነቱ አካል እንዳልሆነች እየተናገሩ ነው።
እስራኤል የተኩስ አቁሙ በተደረሰ ማግሥት ረቡዕ ዕለት በከፈተችው መጠነ ሰፊ ጥቃት ከ300 በላይ ሰዎች ሲገደሉ፤ ከአንድ ሺህ በላይ ቆስለዋል። እስራኤል አሁንም የደቡባዊ ሊባኖስን ሰፊ መሬት ተቆጣጥራ ይዛለች።
የእስራኤሌ ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንጃሚን ኔታንያሁ ከሊባኖስ መንግሥት ጋር ቀጥተኛ ድርድር እንደሚደረግ ቢናገሩም፤ “ሊባኖስ ውስጥ ተኩስ አቁም አይኖርም” ሲሉ ጥቃቶች እንደሚቀጥሉ አመልክተዋል።