የደቡባዊ ሊባኖስ ነዋሪዎች ወደ ቤታቸው ሲመለሱ ያገኙት ፍርስራሽ መሆኑን የተመድ ኃላፊ ተናገሩ
ባለፈው ሳምንት መጨረሻ ሊባኖስ እና እስራኤል ተኩስ አቁም ለማድረግ ከተስማሙ በኋላ “ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው” የደቡባዊ ሊባኖስ ነዋሪዎች ወደ መኖሪያቸው ቢመለሱም፤ መንደራቸው ሲደርሱ ያገኙት “ፍርስራሽ” መሆኑን የተባበሩት መንግሥታት የሰብአዊ ጉዳዮች ኃላፊ ቶም ፍሌቸር ተናገሩ።
ፍሌቸር ከቢቢሲ ‘ቱዴይ’ የራዲዮ ፕሮግራም ጋር በነበራቸው ቆይታ፤ “ሸቀጦችን እናጓጉዝባቸው ከነበሩ ስድስት ድልድዮች ውስጥ አምስቱ ወድመዋል፤ ስለዚህ አሁን እርዳታ ለማግኘት የምናደርገውን ጥረት ብቻ ሳይሆን ሲቪል ሰዎች [ወደ ቤታቸው] ለመመለስ የሚያደርጉትን እንቅስቃሴ የበለጠ ውስብስብ አድርጎታል” ብለዋል።
የተባበሩት መንግሥታት ምግብ፣ መድኃኒት እና ብርድ ልብሶችን የጫኑ ሁለት ተሽከርካሪዎችን በሳምንቱ መጨረሻ ወደ አካባቢዎቹ ማድረስ መቻሉን ገልጸዋል።
ተኩስ አቁም ከመደረጉ አስቀድሞ እስራኤል በሊታኒ ወንዝ ላይ የተዘረጉት እና ደቡባዊ ሊባኖስን ከቀሪው አገሪቱ ክፍል ጋር የሚያገናኙ ድልድዮች ላይ ለሳምንታት ጥቃት ስትፈጽም ቆይታለች።
እስራኤል ድልድዮቹን የመታችው የሄዝቦላህ ኃይሎችን እና እንቅስቃሴያቸውን ዒላማ በማድረግ መሆኑን ትናገራለች።