የአሜሪካ ጦር የኢራን ወደቦችን ከሰኞ ጀምሮ እንደሚዘጋ ገልጾ ነገር ግን በወሽመጡ ላይ ወደ ሌላ አገራት የሚንቀሳቀሱ መርከቦቸን ላይ “መስተጓጎል እንደማይፈጥር” አስታውቋል።
ትራምፕ በበኩላቸው በዋሺንግተን አቅራቢያ በሚገኘው የአንድሪው የጦር ሠፈር ለጋዜጠኞች ኢራን ወደ ድርድሩ ባትመለስ “ምንም እንደማይሰማቸው” ተናግረዋል።
“ተመለሱ አልተመለሱ ግድ አይሰጠኝም። ካልተመለሱም ችግር የለብኝም” ብለዋል።
ትራምፕ ይህንን ያሉት በሁለቱ አገራት መካከል በፓኪስታን ኢዝላማባድ የተደረገው የቀጥታ ንግግር ሳይሳካ ከቀረ በኋላ ነው።
ትራምፕ በሁለቱ አገራት መካከል የተደረሰው የተኩስ አቁም “በመልካም ሁኔታ እንደቀጠለ” መሆኑን ተናግረዋል።
የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ ወደ ኢራን ወደቦች የሚገቡ እና የሚወጡ መርከቦችን ሰኞ ዕለት ከ11 ሰዓት ጀምሮ (14:00 GMT) እንደሚዘጋ አስታውቋል።
የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ኢራን “ሆን ብላ” የሆርሙዝ ወሽመጥን ዳግም ሳትከፍት ቀርታለች ካሉ በኋላ ወደቦቹ አንዲዘጉ አዝዘዋል።
ፕሬዚዳንቱ የአሜሪካ ባሕር ኃይል ላይ ጥቃት ለመፈጸም የሚሞክር “መዓት እንደሚወርድበት” አስታውቀው ማንኛውም መርከብ በወሽመጡ ላይ ለማለፍ ቀረጥ እንዳይከፍል አስታውቀዋል።
በአሜሪካ እና በኢራና መካከል በፖኪስታን የተደረገው ድርድር ሳይሳካ ቀርቶ ዳግም የተፈጠረውን ውጥረት ተከትሎ የነዳጅ ዘይት ዋጋ በበርሜል ከ100 ዶላር በላይ መሸጥ ጀምሯል።
ትራፕም ከኢራን ጋር የተደረገው የቀጥታ ንግግር ያልተሳካለው “ኢራን የኒውክሌር ፍላጎቷን ለመተው ፈቃደኛ ሳትሆን ስለቀረች ነው” ሲሉ ወንጅለዋታል።
የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራጋቺ በበኩላቸው ቴህራን “በቀና ልብ” በድርድሩ ላይ መሳተፏን ሲናገሩ የኢራን ፓርላማ አፈ ጉባዔ ሞሐመድ ባጋር ጋልቢፍ ደግሞ ኢራን “ለማስፈራሪያዎች አትንበረከክም” ብለዋል።
የኢራን አብዮታዊ ዘብ ወደ ወሽመጡ የሚጠጉ መርከቦች የተኩስ አቁሙን እንደጣሱ ይቆጠራሉ ሲል አስጠንቅቋል።