ቀጥታ, የአሜሪካ ጦር ከዛሬ ጀምሮ የኢራን ወደቦችን እንደሚዘጋ ሲገልጽ ትራምፕ ቴህራን ወደ ድርድሩ ባትመለስ “ግድ እንደማይሰጣቸው” ተናገሩ

የአሜሪካ ጦር የኢራን ወደቦችን ከሰኞ ጀምሮ እንደሚዘጋ ገልጾ ነገር ግን በወሽመጡ ላይ ወደ ሌላ አገራት የሚንቀሳቀሱ መርከቦቸን ላይ “መስተጓጎል እንደማይፈጥር” አስታውቋል። ትራምፕ በበኩላቸው በዋሺንግተን አቅራቢያ በሚገኘው የአንድሪው የጦር ሠፈር ለጋዜጠኞች ኢራን ወደ ድርድሩ ባትመለስ “ምንም እንደማይሰማቸው” ተናግረዋል።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. የኢራን ጦር የአሜሪካ እርምጃ ‘የባሕር ላይ ውንብድና’ ነው አለ

    የኢራን ወታደራዊ ኃይል ዋሽንግተን የኢራን ወደቦችን ለመዝጋት ያሳለፈችው ውሳኔ ሕገ ወጥ እና የባሕር ላይ ውንብድና ነው አለ።

    ጦሩ የአጸፋ እርምጃ እንደሚወስድም ዝቷል።

    በአገሪቱ ብሔራዊ የዜና አገልግሎት በኩል በታተመ መግለጫ ኢራን የሆርሙዝ ወሽመጥን መቆጣጠሯን ትቀጥላለች ያለ ሲሆን፤ ጦርነቱ ቢቋጭ እንኳ ከጠላት ጋር ግንኙነት ያላቸው መርከቦች በኢራን የውሃ ግዛት ላይ የመተላለፍ መብት የላቸውም ብሏል።

    የኢራን ጦር ሌሎች የባሕረ ሰላጤው አገራትን በማስጠንቀቅ፤ በቀጣናው የወደቦች ደኅንነት “ለሁሉም አልያም ለማንም አይሆንም” ብሏል።

    የኢራን ወደቦች በአሜሪካ ዒላማ ከሆኑ “በፋርስ ሰላጤ እና በኦማን ባሕር ማንም ደኅና አይሆንም” በማለት አስጠንቅቋል።

  2. የባሕር መስመርን መዝጋት ምን ማለት ነው? እንዴትስ ይሰራል?

    በአሜሪካ እአአ በ2022 የወጣው ሕግ የባሕር መስመርን መዝጋት “የሁሉም አገራት መርከቦች እና/ወይም አውሮፕላኖች፣ ጠላት እና ገለልተኛ ወገኖች፣ ወደተለዩ ወደቦች፣ አየር ማረፊያዎች፣ ወይም የባህር ዳርቻ አካባቢዎች በጠላት አገር ቁጥጥር ስር ያሉ ቦታዎች እንዳይገቡ ወይም እንዳይወጡ ለመከላከል የሚደረግ የጦር እንቅስቃሴ" በማለት ይበይነዋል።

    የአሜሪካ ባሕር ኃይል በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ የሚያካሄዳቸውን ዘመቻዎች ይህንን ሕግ የተከተለ ይመስላል።

    የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ (ሴንቲኮም) የኢራን ወደቦችን እንደሚዘጋ በመግለጽ ባወጣው መግለጫ ላይ “ከሁሉም በባሕረ ሰላጤው እና በኦማን ባህረ ሰላጤ ከሚገኙ የኢራን ወደቦች በሚነሱ በሁሉም አገራት መርከቦች ላይ ያለምንም ልዩነት ተግባራዊ የሚሆን” መሆኑን ጠቅሷል።

    ሴንቲኮም ከኢራን ወደቦች ውጭ የሚመጡ መርከቦች በወሽመጡ በኩል ማለፍ እንደሚችሉ እና ክልከላ እንደማይደረግባቸው አስታውቋል።

    የንግድ የባሕር ትራንስፖርት አገልግሎት ሰጪዎችም መስመሩ ከመዘጋቱ በፊት እንዲያውቁት እንደሚደረግ ተናግሯል።

    ፕሬዚዳንት ትራምፕ በወሽመጡ የሚገኙ የኢራን ወደቦችን በመዝጋት ሌሎች አገራትም እንደሚሳተፉ ገልጸዋል። ነገር ግን ይሳተፋሉ ያሏቸውን አገራት በስም አልጠቀሱም።

    ቢቢሲ ዩናይትድ ኪንግደም በዚህ ዘመቻ ላይ እንደማትሳተፍ ማወቅ ችሏል።

  3. አሜሪካ እዘጋቸዋለሁ ያለችው የኢራን ወደቦች እና ተጽዕኗቸው

    አሜሪካ እና ኢራን በፓኪስታን የሰላም ስምምነት ላይ መድረስ ባለመቻላቸው ዶናልድ ትራምፕ አሜሪካ በሆርሙዝ ወሽመጥ የሚገቡ እና የሚወጡ መርከቦችን እንደምታግድ አስታውቀዋል።

    የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ (ሴንትኮም) የአሜሪካ ኃይል ባሕረ ሰላጤውን ጨምሮ ወደ ኢራን ወደቦች በሚገቡ እና በሚወጡ መርከቦች ላይ “ያለ ልዩነት” እገዳውን እንደሚያስፈፅም ገልጿል።

    ይሁን እንጂ ሴንትኮም የአሜሪካ ኃይሎች ከኢራን ወደቦች ውጭ በሚደረገው የመርከቦች ነፃ እንቅስቃሴ ላይ እንቅፋት እንደማይሆን አስታውቋል።

    በትሩዝ ሶሻል የማኅበራዊ ትስስር ገፅ ትራምፕ አሜሪካ ከሠኞ ጀምሮ በኢራን ወደቦች መርከቦች እንዳይንቀሳቀሱ እንደምትዘጋ ተናግረዋል።

    የመከላከያ ተንታኞች ይህ የአሜሪካ እርምጃ ኢራን ነዳጅ እንዳትሸጥ ያደርጋል ብለዋል።

    ጀስቲን ክራምፕ የተባሉ ተንታኝ የኢራንን ወደቦች ለመዝጋት ትራምፕ የያዙት እቅድ የኢራንን ጦርነት የበለጠ የሚያባብስ እና ስምምነት ባለመደረሱ “የትራምፕን ብስጭት የሚያንፀባርቅ” ነው ብለውታል።

    ዕቅዱ እንደ ቻይና ላሉ አገራት ኢራን ነዳጇን እንዳትሸጥ የሚያግድ ሲሆን፤ ይህም ኢራን ላይ ጫና ያሳድራል።

    አሜሪካ እና ኢራን አንዳቸው በሌላኛቸው ላይ የተሻለ የመደራደሪያ አቅም እንዳላቸው ያምናሉ ሲሉ የጠቆሙት ተንታኙ፤ ሁለቱም አገራት ማሸነፋቸውን ሌላውን ዝቅ በማድረግ ለማሳየት እየሞከሩ ነው ብለዋል።

    ይህም የበለጠ ውጥረት እና ውድመት እንደሚያስከትል ጠቁመው፤ በሳምንቱ መገባደጃ የተደረገው ድርድር ምንም እንኳ ፍሬ ባያፈራም “አዎንታዊ ተፅዕኖ” አሳድሯል የሚል ስሜት እንዳላቸውን ተናግረዋል።

    “ሰፊ ውይይት ማድረጋቸው መልካም ነው። የሚያወያይ ምንም ነገር ባይኖር ኖሮ ድርድሩ በፍጥነት ይጠናቀቅ ነበር” ብለዋል።

  4. የፕሬዝዳንት ትራምፕ ቀጣይ እርምጃ አሜሪካ ላይ የፈጠረው ስጋት

    በምክትል ፕሬዝዳንት ጄዲ ቫንስ የተመራው የዲፕሎማት ቡድን ጦርነቱን ለማስቆም የሚያስችል ስምምነት ለማድረግ ሞክሮ ከከሸፈ በኋላ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ የሚቀጥለው እርምጃቸውን ወስነዋል።

    ይህን ውሳኔያቸውም እሁድ ዕለት ትሩዝ ሶሻል በተባለው ማኅበራዊ ትስስራቸው በተከታታይነት በለጠፏቸው ጽሑፎች ይፋ አድርገዋል።

    ትራምፕ አሜሪካ በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ ሚደረግ የመርከብ እንቅስቃሴ ታግዳለች ሲሉ ጽፈዋል።

    “ሕገ ወጥ ቀረጥ የከፈለ ሁሉ በባሕር ደኅንነት ያለው ጉዞ አያደርግም” ብለዋል።

    አሜሪካ ለአገራት የመርከብ ጉዞ ደኅንነት ለማረጋገጥ በሆርሙዝ ወሽመጥ ባሕር ውስጥ የተጠመዱ ፈንጂዎችን ማፅዳቷን ትቀጥላለችም ብለዋል።

    የአሜሪካ ጦር ለዚህ መዘጋጀቱን የጠቆሙት ትራምፕ “በተገቢው ወቅት” ኢራን ላይ ጥቃታቸውን ለመቀጠል ዝግጁ መሆናቸውንም ገልፀዋል።

    በፓኪስታን ኢስላማባድ ለ20 ሰዓታት የተደረገው ድርድር መሻሻል የታየበት መሆኑን ቢጠቅሱም ትራምፕ ኢራን የኒውክሌር ልማቷን እንድትገታ አሜሪካ ያስቀመጠችውን አቋም አታሟላም ብለዋል።

    የትራምፕ ልጥፎች ምንም እንኳ ባለፈው ሳምንት የኢራንን ሥልጣኔ ከምድረ ገፅ አጠፋለሁ እንደሚለው አውዳሚ ባይሆኑም እርምጃዎቹ በርካታ አዲስ ስጋቶችን ያዘሉ ናቸው። ለአሜሪካም ስጋት ነው።

    የባሕር ፈንጂዎችን ማፅዳት የአሜሪካ መርከቦች በኢራን እንዲጠቁ የበለጠ ተጋላጭ አያደርጋቸውም? አሜሪካ የኢራንን የመተላለፊያ ክፍያ ማን እንደሚከፍል በምን ልታውቅ ትችላለች? የመርከብ እግዱን የጣሱ የውጭ አገር ሰንደቅ ዓላምን በሚያውለበልቡ መርከቦች ላይ ኃይል ልትጠቀም ትችላለች? እንደ ቻይና ያሉ በኢራን ነዳጅ ላይ ጥገኛ የሆኑ አገሮች ምን ዓይነት ምላሽ ይሰጣሉ? የኢራንን ዋነኛ የገቢ ምንጭን ለማድረቅ የተወሰደው እርምጃ የነዳጅ ዋጋን ከዚህም በላይ ያንረዋል?

    ለእነዚህ መሠረታዊ ጥያቄዎች ግልፅ ምላሽ የለም።

  5. የዓለም የነዳጅ ዋጋ ዳግም ከ100 ዶላር በላይ ከፍ አለ

    በአሜሪካ እና በኢራን መካከል የተደረገው ድርድር ያለ ስምምነት መጠናቀቁን ተከትሎ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ የኢራንን ወደቦች እንደሚዘጉ ከዛቱ በኋላ የነዳጅ ዋጋ በበርሜል ከ100 ዶላር በላይ አሻቀበ።

    የዓለም ነዳጅ ዋጋን የሚተምነው የብሬንት ድፍድፍ ነዳጅ ዘይት በ7.3 በመቶ ጭማሪ በማሳየት 102.30 ዶላር ተሸጧል።

    በሳምንቱ መጨረሻ ላይ የተደረገው ድርድር አለመሳካቱ የዓለም የኃይል ቀውስ እየተባባሰ ሊሄድ ይችላል የሚል ስጋትን አስነስቷል።

    ባለፈው ረቡዕ ዋሽንግተን እና ቴህራን የሆርሙዝ የባሕር ወሽመጥ የንግድ መተላለፊያን ለመክፈት የሁለት ሳምንት የተኩስ አቁም ስምምነት ላይ ከደረሱ በኋላ የነዳጅ ዋጋ ከ100 ዶላር በታች ወርዶ ነበር።

  6. የሆርሙዝ ወሽመጥ ለምን የዓለማችን ቁልፍ የባሕር መስመር ሆነ?

    የሆርሙዝ ወሽመጥ በዓለም ላይ በጣም አስፈላጊው የስትራቴጂክ የኃይል መስመር ነው።

    የፋርስ ባሕረ ሰላጤን ከአረብ ባሕር ጋር ያገናኛል። በዓለም 39 በመቶ የሚሆነውን የባሕር ድፍድፍ ነዳጅ እና 19 በመቶው የተፈጥሮ ጋዝ ይተላለፍበታል።

    ከአብዛኛዎቹ ስትራቴጂካዊ መስመሮች በተለየ የባሕረ ሰላጤው አገራት ምርታቸውን የሚልኩበት ከሆርሙዝ ውጪ ሌላ አማራጭ የላቸውም።

    ኢራን ከ1980ዎቹ ጀምሮ የሆርሙዝ ወሽመጥን እንደምትዘጋ በየጊዜው ስታስፈራራ ቆይታለች።

    አሜሪካ እና እስራኤል በኢራን ግዛት ላይ የመጀመሪያውን የአየር ድብደባ ካከሄዱበት ቀን ጀምሮ የተከሰተው የመርከብ መስተጓጎል ግን በአስርት ዓመታት ውስጥ እጅግ የከፋው መሆኑ ተነግሯል።

    ይህ ክስተት በታሪክ ውስጥ ከፍተኛውን የነዳጅ አቅርቦት መስተጓጎል ከማስከተሉም በላይ በዓለም አቀፍ የድፍድፍ ነዳጅ ዋጋ ላይ አስደንጋጭ ጭማሪ ፈጥሮ ቆይቷል።

    በባሕረ ሰላጤው ውስጥ የተፈጠረው መስተጓጎል ከኢነርጂ ዘርፉ በላይ ተጽዕኖ አሳድሯል። የአካባቢው አገራት በየዓመቱ ከ26 ሚሊዮን በላይ ኮንቴይነሮችን ያስተናግዳሉ። ከፍተኛ መጠን ያለው ማዳበሪያም በዚሁ መንገድ ያልፋል።

    በወሽመጡ ለረጅም ጊዜ የሚቆይ ጉዞ መስተጓጎል ከተፈጠረ በዓለም አቀፍ የምግብ ምርቶች ላይ ቀጥተኛ ተጽዕኖ ይኖረዋል።

  7. ትራምፕ በኢራን ላይ ዳግም ጥቃት ለመክፈት እያጤኑ መሆኑን ዎል ስትሪት ጆርናል ዘገበ

    አሜሪካ እና ኢራን በፓኪስታን ያካሄዱት ድርድር ሳይሳካ መቅረቱን ተከትሎ ትራምፕ ቴህራን ላይ ዳግም ጥቃት የመክፈት ሃሳብ እንዳላቸው ዎል ስትሪት ጆርናል ዘገበ።

    ዎል ስትሪት ጆርናል ስማቸውን ያልገለጻቸው የአሜሪካ ባለሥልጣናትን ጠቅሶ ከሌሎች እርምጃዎች በተጨማሪ ኢራን ላይ ድብደባ ለመጀመር እያጤኑ መሆኑን ዘግቧል፥።

    ትራምፕ እሁድ ዕለት የባሕር ኃይላቸው የሆርሙዝ ወሽመጥን እንዲዘጋ ትዕዛዝ ሰጥተዋል።

    ዋይት ሐውስ ቢቢሲ ስለ ጋዜጣው ዘገባ ላቀረበው ጥያቄ ሁሉም አማራጮች ጠረጴዛ ላይ ናቸው ሲል ምላሽ ሰጥቷል።

    የዋይት ሐውስ ቃል አቀባይ ኦሊቪያ ዌልስ “ፕሬዚዳንቱ የሆርሙዝ ወሽመጥን እንዲዘጋ ባሕር ኃይሉን አዝዘዋል። የኢራንን ዝርፊያ ያበቃል እና ሁሉንም ተጨማሪ አማራጮች በጠረጴዛው ላይ ተቀምጠዋል። ለዎል ስትሪት ጆርናል ፕሬዚዳንቱ ቀጥሎ የሚያደርጉትን መረጃውን የሰጠ ማንኛውም ሰው በግልጽ ግምቱን ነው ያስቀመጠው” ብለዋል።

  8. ትራምፕ ኢራን አሁንም የኒውክሌር ጦር መሣሪያ ትፈልጋለች አሉ

    ኢራን እና አሜሪካ ያካሄዱት ድርድር ያለ ምንም ስምምነት ከተጠናቀቀ በኋላ ትራምፕ ቴህራን አሁንም የኒውክሌር ጦር መሣሪያ ፍላጎት አላት ሲሉ ተናገሩ።

    የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ኢራን አሁንም የኒውክሌር ፍላጎት እንዳላት በኢዝላማባድ ድርድር ወቅት መናገሯን ጠቅሰዋል።

    “አሁንም ይፈልጋሉ፤ ይህንን ደግሞ የዚያን ዕለት ምሽት [ድርድር በተካሄደበት ዕለት] ግልጽ አድርገዋል። ኢራን የኒውክሌር ጦር መሣሪያ ሊኖራት አይችለም።”

    ከዚህ በፊት ትራምፕ ከቴህራን ጋር ያደረጉት የቀጥታ ንግግር ያልተሳካውቴህራን “የኒውክሌር ፍላጎቶቿን ለመተው ፈቃደኛ ሳትሆን ስለቀረች ነው” ብለዋል።

    የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራጋቺ በበኩላቸው ሁለቱ አገራት ከስምምነት ለመድረስ “ስንዝር ቀርቷቸው ነበር” ካሉ በኋላ ነገር ግን አገራቸው “የተለጠጠ ፍላጎት፣ የግብ ለውጥ፣ የወደብ መዝጋት” እንደገጠማት ተናግረዋል።

  9. አሜሪካ የኢራን ወደቦቸን ከሰኞ ጀምሮ እንደምትዘጋ አስታወቀች

    የአሜሪካ ጦር የኢራን ወደቦችን ከሰኞ ጀምሮ እንደሚዘጋ ገልጾ ነገር ግን በወሽመጡ ላይ ወደ ሌላ አገራት የሚንቀሳቀሱ መርከቦቸን ላይ “መስተጓጎል እንደማይፈጥር” አስታውቋል።

    ትራምፕ በበኩላቸው በዋሺንግተን አቅራቢያ በሚገኘው የአንድሪው የጦር ሠፈር ለጋዜጠኞች ኢራን ወደ ድርድሩ ባትመለስ “ምንም እንደማይሰማቸው” ተናግረዋል።

    “ተመለሱ አልተመለሱ ግድ አይሰጠኝም። ካልተመለሱም ችግር የለብኝም” ብለዋል።

    ትራምፕ ይህንን ያሉት በሁለቱ አገራት መካከል በፓኪስታን ኢዝላማባድ የተደረገው የቀጥታ ንግግር ሳይሳካ ከቀረ በኋላ ነው።

    ትራምፕ በሁለቱ አገራት መካከል የተደረሰው የተኩስ አቁም “በመልካም ሁኔታ እንደቀጠለ” መሆኑን ተናግረዋል።

    የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ ወደ ኢራን ወደቦች የሚገቡ እና የሚወጡ መርከቦችን ሰኞ ዕለት ከ11 ሰዓት ጀምሮ (14:00 GMT) እንደሚዘጋ አስታውቋል።

    የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ኢራን “ሆን ብላ” የሆርሙዝ ወሽመጥን ዳግም ሳትከፍት ቀርታለች ካሉ በኋላ ወደቦቹ አንዲዘጉ አዝዘዋል።

    ፕሬዚዳንቱ የአሜሪካ ባሕር ኃይል ላይ ጥቃት ለመፈጸም የሚሞክር “መዓት እንደሚወርድበት” አስታውቀው ማንኛውም መርከብ በወሽመጡ ላይ ለማለፍ ቀረጥ እንዳይከፍል አስታውቀዋል።

    በአሜሪካ እና በኢራና መካከል በፖኪስታን የተደረገው ድርድር ሳይሳካ ቀርቶ ዳግም የተፈጠረውን ውጥረት ተከትሎ የነዳጅ ዘይት ዋጋ በበርሜል ከ100 ዶላር በላይ መሸጥ ጀምሯል።

    ትራፕም ከኢራን ጋር የተደረገው የቀጥታ ንግግር ያልተሳካለው “ኢራን የኒውክሌር ፍላጎቷን ለመተው ፈቃደኛ ሳትሆን ስለቀረች ነው” ሲሉ ወንጅለዋታል።

    የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራጋቺ በበኩላቸው ቴህራን “በቀና ልብ” በድርድሩ ላይ መሳተፏን ሲናገሩ የኢራን ፓርላማ አፈ ጉባዔ ሞሐመድ ባጋር ጋልቢፍ ደግሞ ኢራን “ለማስፈራሪያዎች አትንበረከክም” ብለዋል።

    የኢራን አብዮታዊ ዘብ ወደ ወሽመጡ የሚጠጉ መርከቦች የተኩስ አቁሙን እንደጣሱ ይቆጠራሉ ሲል አስጠንቅቋል።

Trending Now